Sunday, June 14, 2015

በአዲስ አበባ የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ለማስቀረት አንድ ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋል 14June2015 -  ሰኔ 7, 2007 ዓ.ም.

መነሻ ገጽ - ዜና - በአዲስ አበባ የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ለማስቀረት አንድ ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋል
በአዲስ አበባ የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ለማስቀረት አንድ ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋልዋና ዜና
14 JUNE 2015 ተጻፈ በ  

በአዲስ አበባ የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ለማስቀረት አንድ ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋል

በአዲስ አበባና በዙሪያዋ የሚገኙ 12 የኦሮሚያ ክልል ልዩ ዞን ከተሞች በየጊዜው የሚገጥማቸውን የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ለማስቀረት ማስተር ፕላን ተነደፈ፡፡ አዲሱን ማስተር ፕላን ተግባራዊ ለማድረግ አንድ ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋል፡፡
‹‹አዲስ አበባና ዙሪያዋ የኤሌክትሪክ ዲስትሪቢውሽን ማስተር ፕላን ጥናት ፕሮጀክት›› በሚል ስያሜ የተነደፈው ማስተር ፕላን፣ በሚቀጥሉት 20 ዓመታት በአጭር፣ በመካከለኛና በረዥም ጊዜ ተግባራዊ ይደረጋል ተብሏል፡፡ 
ባለፈው ሐሙስ ሰኔ 4 ቀን 2007 ዓ.ም. በማስተር ፕላኑ ላይ ውይይት በተደረገበት ወቅት፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አዜብ አስናቀ እንደተናገሩት፣ እ.ኤ.አ. እስከ 2017 ድረስ ተግባራዊ በሚደረገው የአጭር ጊዜ ዕቅድ አሮጌ ኤሌክትሪክ ማስተላለፊያ መስመሮችና ማከፋፈያ ጣቢያዎች ይለወጣሉ፡፡ 
በአጠቃላይ ፕሮጀክት ተግባራዊ ለማድረግ አንድ ቢሊዮን ዶላር በጀት መያዙ ተገልጿል፡፡ ከዚህ ውስጥ እ.ኤ.አ. እስከ 2017 ለሚተገበረው የአጭር ጊዜ ዕቅድ ማስፈጸሚያ 285 ሚሊዮን ዶላር፣ እ.ኤ.አ. ከ2018 እስከ 2022 ተግባራዊ ለሚሆነው መካከለኛ ዘመን ዕቅድ ማስፈጸሚያ 37 ሚሊዮን ዶላር፣ ለረዥም ጊዜ ዕቅድ ማስፈጸሚያ (እ.ኤ.አ. ከ2023 እስከ 2034) 745 ሚሊዮን ዶላር መበጀቱ ተገልጿል፡፡ 
በአጠቃላይ በአዲስ አበባና አካባቢው የኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎትና ዕድገት ለማጣጣም የተያዘውን ዕቅድ ለማስፈጸም፣ 1,067 ቢሊዮን ዶላር ይፈጃል ተብሎ ተገምቷል፡፡ 
ፕሮጀክቱ ተግባራዊ የሚደረገው በአዲስ አበባ በሚገኙት አሥር ክፍላተ ከተሞችና በኦሮሚያ ልዩ ዞን በሚገኙት አዲስ ዓለም፣ ኢሉ፣ ወልመራ፣ ሙሎ፣ ሱሉልታ፣ በረህ፣ አሌልቱ፣ ጊምቢቹ፣ አደአ፣ አቃቂ፣ ዓለም ገና፣ ቀርሳና ማሊሞ ወረዳዎች ናቸው፡፡ 
አዲስ አበባና ዙሪያዋ አገሪቱ ከምታመነጨው የኤሌክትሪክ ኃይል ውስጥ 60 በመቶውን እንደሚጠቀሙ ኢንጂነር አዜብ ገልጸው፣ አካባቢዎቹ የሚያጋጥማቸውን የኤሌክትሪክ ኃይል ሥርጭት መቆራረጥ ለማስቀረት የፕሮጀክቱ ተግባራዊ መሆን ወሳኝ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ 
ይህንን ማስተር ፕላን ከአፍሪካ ልማት ባንክ በተገኘ 3.5 ሚሊዮን ዶላር ያጠናው የእንግሊዝ ኩባንያ የሆነው ፓርሳን ብሪንኤርሆፍ ሊሚትድ ነው፡፡ የኩባንያው ተወካይ ናንካ ብሩስ በውይይቱ ላይ እንደተናገሩት፣ አዲስ አበባ በፍጥነት እያደገች በመሆኑ እያጋጠማት ካለው የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ወጥታ፣ ለዕድገቷ የሚያስፈልጋትን ኃይል ለማግኘት ማስተር ፕላኑ ጠቀሜታው የጎላ ነው፡፡ 
ይህ ፕሮጀክት ተግባራዊ ሲሆን፣ በከተማው የሚገኙ አሮጌ የኃይል ማስተላለፊያ መስመሮችና ማከፋፈያዎች በአዲስ ይተካሉ፡፡ መሻሻል ያለባቸውም እንዲሻሻሉ ይደረጋል በማለት ኢንጂነር አዜብ ተናግረዋል፡፡ 
በቀጣይነት ይህ ፕሮጀክት በሐዋሳ፣ በመቐለ፣ በባህር ዳርና በሌሎች ትልልቅ የክልል ከተሞች ተግባራዊ እንደሚሆን ኢንጂነር አዜብ አስረድተዋል፡፡ 
በአዲስ አበባና በአካባቢው ለረጅም ጊዜ እያጋጠመ ያለው የኃይል መቆራረጥ፣ በዋናነት በኤሌክትሪክ ኃይል ማስተላለፊያና ማሠራጫ ጣቢያዎች እርጅና ምክንያት ነው ሲባል ቆይቷል፡፡ ነገር ግን ከቅርብ ወራት ወዲህ ለኃይል መቆራረጡ የበልግ ዝናብ በተፈለገው መጠን ባለመዝነቡ ምክንያት፣ ግድቦች በቂ ውኃ ባለመያዛቸው እንደሆነ ባለሙያዎች እየተናገሩ ነው፡፡                                         ምንጭ ሪፐርተር ጋዜጣ

No comments: