Friday, April 8, 2016

እሪይ በይ ሀገሬ

ኢትዮጵያ በተፈጥሮ የታደለች ግን ከዓለም በጣም ደሃ ተብለው ከሚመደቡት ውስጥ የመጨረሻው ጠርዝ ላይ የሰፈረች፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠረው በርሃብና ቸነፈር ለረጅም ዓመታት የሚሰቃይና የውጭ አገር እርዳታ እጅ ጠብቆ የሚያድር ሕዝብ የሚኖርባት አገር ናት።ከድህነቱ በተጨማሪም ባለመረጋጋት፣የሕዝብ መብት የተረገጠባትና አምባገንን የሚፈነጭባት ከመሆኑ አንጻር የመጀመሪያውን ቦታ ይዛ ትገኛለች።በየእለቱ የመረጋጋትና የሰላም ኑሮ እየጨለመ የመጣባት፣ስጋት የሰፈነባት፣ ሕዝቡ በጎሳ ተከፋፍሎ በጠላትነት እንዲጋጭና እንዲተያይ የሚያደርግ ጎሰኛ ቡድን ስልጣኑን ይዞ ያሻውን የሚያደርግባት አገር ነች። ይህም ብቻ አይደለም በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ ሰርቶ አዳሪው በተለይም ከተሜው አንድ ጊዜ በቀን እህል ቀምሶ ለማደር የማይችልበት ደረጃ ላይ ደርሷል።የገበያ ዋጋ ሰው ገዝቶ ከሚችልበት አቅም በላይ እየሆነ የበይ ተመልካችና ለጥቂቶች ገነት ለብዙሃኑ ሲኦል የሆነች አገር ሆናለች።
አገሪቱ በእድገት እየመጠቀች ነው ተብሎ ቢለፈፍም የሕዝቡ ኑሮ ያው በገሌ ነው።ብስቁል ፊቱና የሰውነት ቅርጹ፣ከአለባበሱ ጋር ሲታይ በሃያአንደኛው ክፍለዘመን ውስጥ የሚኖር አይመስልም።
በከተማና በገጠር የውሃና የሃይል ምንጭ አለመሟላት፣የመገናኛ መስመር በብቃት አለመዘርጋት፣ መሪዎች ተለዋወጡባት እንጂ በአገሪቱ አጠቃላይ ገጽ ላይ ለውጥ እንዳልመጣ በጉልህ ይታያል። አደገኛ የመኪና መንገድ ካለባቸው አገሮች መካከል በአንደኛ ደረጃ የተመደበች አገር በመሆኗ በአደጋ የሚሞተውና አካለ ጎደሎ የሚሆነው ቁጥሩ ከፍተኛ ነው። ወጣቱ ስራ አጥ በመሆኑ ለመኖር ሲል ወደ ውጭ ለመሰደድና በአደገኛ ተግባር ላይ ለመሰማራት የሚሻው ቁጥር እየጨመረ እንጂ እየቀነሰ አልመጣም። በመንግሥት የመልካም አስተዳደር አለመኖር “ተከተል አለቃህን” ሆኖ በሕዝቡ ላይ የመልካም ምግባር ድህነትን አስፍኗል።መሪዎቹ ቢለዋወጡም በአገሪቱ ላይ መሰረታዊ የስርዓት ለውጥ አልመጣም።
አሁን ስለራሱ እንጂ ስለአገርና ወገኑ ቀርቶ ስለቤተሰቡ የሚያስበውና የሚጨነቀው እየተመናመነ መጥቷል።ብሔራዊ ስሜት ፣የአገር ፍቅር፣ቀናነትና፣መቻቻል ያለፈበት ተረት ሆኖ በቦታው አጭበርባሪነት፣ዘረፋ፣ውሸት፣ጎሰኝነት የዘመኑ እውቀት እየሆነ መጥቷል።
በመንግሥትና በደጋፊዎቹ የሚታየው የኑሮ ለውጥ ለአገሪቱና ለሕዝቡ ኑሮ መመዘኛ ሊሆን አይችልም።በስርዓቱ ባለቤቶች ከሚፈጸመው ጸረ ሕዝብ ወንጀሎች ጎልቶ የሚታየው የአገሪቱን ቅርስና ንብረት በተለይም ለእርሻና ለቤት መስሪያ የሚሆኑትን የገጠርና የከተማ መሬቶች ከሕዝቡ እየቀማ የንግድ ሸቀጥ በማድረግ የሚካሄደው ዘረፋ ነው። ሕዝብ ለዓመታት በውርስና በግዢ የኖረበትን ቦታ እየቀሙ በማይችለው የዋጋ ተመን መልሶ እንዲገዛ ካልቻለም ለቆ እንዲሄድና ቤት አልባ እንዲሆን በማስገደድ ቦታው ለሚችል እየተሸጠ ገንዘብ በመሰብሰብ የሚካሄደው የማፍያ ስራ በየእለቱ እየጨመረ በመሄድ ላይ ነው።የቀን ገቢው በአማካኝ አንድ የአሜሪካ ዶላር በሆነው ሕብረተሰብ የኤኮኖሚ አቅም በሚሊየን ዶላር የሚገመት ቦታና ቤት ገዝቶ ለመኖር ማን ይችላል፧ ተብሎ ቢጠየቅ ፣መልሱ በስልጣን ላይ ያሉትና ቤተሰቦቻቸው እንዲሁም የውጭ አገር ከበርቴ ዜጎች ብቻ ለመሆናቸው አሰላለፋቸውን ና የባለቤትነት ሰነዶቹን ማየቱ ብቻ ይበቃል።
ተወላጁ ከመሬቱ እየተነቀለ በገዛ አገሩ ስደተኛ ሲሆን፣ሕጻናት የመንገድ ላይ ተዳዳሪ ሲሆኑ፣ቦታቸውን የሚወርሱት መክፈል የሚችሉት የውጭ አገር ከበርቴዎች ፣አረቦች፣ቱርኮች፣ሕንዶች፣…ወዘተ ናቸው።ለዚህም ነው ላለፉት ሶስት ወራት የተካሄደው ሕዝባዊ እንቅስቃሴ ሊነሳ የቻለው።እንቅስቃሴው የሁሉም ኢትዮጵያዊ ብሶት የወለደው እንጂ የአንድ ነጠላ ማህበረሰብ ጉዳት ብቻ ያነሳሳው አይደለም።
አገሪቱ በእድገት ላይ ነች ቢባልም በገሃድ የሚታየው እድገት ሕዝቡን ሰንጎ የያዘው የኑሮ ውድነቱ ብቻ ነው።ለቤት ኪራይ፣ለምግብ፣ለሕክምና ፣ለትምህርት፣ለመጓጓዣ፣ለልብስና ንጽህና …ወዘተ የሚጠየቀው ክፍያ ሕዝቡ ከሚያገኘው ገቢ ጋር የሰማይና የመሬት ያህል ይራራቃል፣እጅግ በጣም አድጓል።ከሌሎቹም አገራት የኑሮ ውድነት ጋር ሲነጻጸር ያስደነግጣል።
ሁኔታውን ተመሳሳይ እድገት ካላቸው ያፍሪካ አገሮች ጋር ለማወዳደር ቢሞከር ሌላውን ትተን በመሬት ዋጋ ያለው ልዩነት አያድርስ ነው።ለዛውም በሌሎቹ መንግሥት የመሬቱ ባለቤት ባልሆነባቸው አገሮች፣በሊዝ ሳይሆን ሙሉ ለሙሉ የባለቤት ይዞታ መብትና እውቅና በሰፈነባቸው አገሮች ጋር ያለውን የዋጋ ተመን ብናስተያየው ሰሚ የለም እንጂ ኡኡ ያሰኛል። የመሬት ባንክ የሚል ፈሊጥ በኢትዮጵያ ካልሆነ በቀር በሌላው አገር አይታወቅም።የባንኩ ባለቤት ደግሞ ሕዝብ ሳይሆን የስልጣኑ ባለቤቶች ናቸው
በመሬት ዙሪያ በኢትዮጵያ ያለው ።በስልጣን ላይ ያለው ቡድን ዳሞትራ እንደምትባለው ባለብዙ አፍ የሸረሪት ዘር በየአቅጣጫው ዘረፋ የሚያከናውንበት ጠንካራ መረብ ዘርግቷል።ይህን የብዝበዛ መረብ ለመበጣጠስና ሕዝቡን ከዚህ የተደራጀ የማፊያ ስርዓት ለመውጣት የተደራጀ ትግል ማካሄድ ያስፈልጋል፤ ሕዝቡም ተባብሮ የተጣለበትን የዋጋ ተመን አልከፍልም ማለት ይገባዋል።በተግባር የሚታየው ግን በተናጠል የባለስልጣኖቹን ፍላጎት እየተቀበለ ማደር ሆኗል፣በጎሳ ተኮር ትግል በተናጠል ለእልቂት መጋለጥ፣መጮህና መርገም መልስ አይሆንም። መንግሥት የዘረጋውን አንድ ለአምስት የስለላ ሰንሰለት ሕዝቡ በግልባጩ አምስት ለአንድ አድርጎ ሊቆጣጠረውና ሊበጣጥሰው ይገባል።ቁርጠኝነት ከብዛት ጋር ሲቀናጅ የሚቋቋመው ሃይል አይኖርም። በውጭ አገር የሚኖረውም ኢትዮጵያዊ ለቁራሽ መሬት ሲል ከአውሬ ስርዓት ጋር እየተባበረ የሕዝቡን ስቃይ ባያበዛው መልካም ነው።የዃላዃላ ከኑግ የተገኘህ ሰሊጥ አብረህ ተወቀጥ መሆን አይቀርም።

No comments: