Tuesday, September 23, 2014

የምእራብ አርማጭሆ ነዋሪዎች በአስተዳዳሪዎች ሽኩቻ ሰዎች እንደሚገደሉ ተናገሩ


መስከረም ፲፪(አሥራ ሁለት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በምዕራብ አርማጮሆ ወረዳ የአብርሃጅራ ነዋሪዎች ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት በተደረገው ህዝባዊ ስብሰባ በመሬት ስሪት ፣በልማት
ና በመልካም አስተዳደር ጉዳዮች ዙሪያ ቅሬታወች ቀርበዋል፡፡በውይይቱ ላይ በመገኘት ቅሬታቸውን ያቀረቡት ነዋሪዎቹ “የወረዳው አመራሮች እርስ በርስ በመሻኮት ስልጣን ለመያዝ ሰዎችን
ያስገድላሉ የበላይ አመራሮችን የኑሮ ሁኔታ በማጥናት ቤት ሰርተዋል፣ሃብት አከማችተዋል በማለት እነርሱም የበላይ አለቆቻቸውን አይነት ያልተገባ ጥቅም ለማግኘት ለሚያደርጉት ጥረት
የሚሯሯጡ እንጅ ለሃገር ተቆርቁረው የሚሰሩ አይደሉም” ሲሉ ተደምጠዋል፡፡
በእያንዳንዱ ቦታ ተገቢ የሆኑ ሰዎች አለመቀመጥም የአመራር ችግር ከመፍጠሩ ባሻገር ‘ ዞን መስተዳድር ላይ ዘመድ አለኝና አሾምህአለሁ ይሄን አምጣ ካልሆነም አባርርሃለሁ ’ ተብሎ
የሚፈከርበት አሰራርና የወረዳ አስተሳሰብ ባላቸው አመራሮች የሚደረግባቸው ጫና እንዳስመረራቸው ተሰብሳቢዎች ገልጸዋል፡፡
ህብረተሰቡ ኢህአዲግን እንዲጠላ የሆነበት ዋና ምክንያት አመራሩ ብቃት የሌለው ከመሆኑ በተጨማሪ በአመራር ላይ የሚያስቀምጣቸው ኃላፊዎች ሰውን በመወንጀል ፣በማሳሰርና
በማስገደል የሚያመኑ በመሆኑ ህብረተሰቡ ወደ አላስፈላጊ ርምጃ የሚከት ከህብረተሰቡ ጋር በመተማመን ወደ መልካም አስተዳደር ለመውሰድ ጥረት የማያደርግ መሆኑንም የተናገሩት
ቅሬታ አቅራቢው ይህ ጉዳይ በጥንቃቄ ታይቶና ተገምግሞ መፍትሄ ልናገኝ ይገባናል ብለዋል፡፡
በሌላ በኩል ቅሬታቸውን ያቀረቡት የአብርሃጅራ ነዋሪዎች ከተማዋ የወረዳ ከተማ ሆና እያለ በፕላኑ መሰረት የመኖሪያ ቤት ካርታ በማግኘት በመብታችን ተጠቃሚ  እንዳንሆን ተደርገናል
በማለት ይናገራሉ፡፡በከተማዋ ትልቁን የኗሪነት ደርሻ የያዘው ህብረተሰብ ፤በቀን ስራ ለረዢም አመት በመስራት ጥሪት የቋጠረው ክፍል ቢሆንም በሰራው ቤት ተበድሮ ተጠቃሚ ለመሆን
የሚያስችለውን መብት በየጊዜው በሚደረግ የምክር ቤት ስብሰባ ተሻረ የሚል ምክንያት በመስጠት ቦታውን ለሚፈልጉት ባለሃብት በሙስና በመሰጠቱ ህብረተሰቡ በመጉላላት ላይ
መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በአካባቢው የሚታረስ በብዙሽህ የሚቆጠር ትርፍ መሬት እያለ መሬት ማግኘት ያልቻሉ ከ400 በላይ ነዋሪዎች እተሰቃዩ ያሉበትን ሁኔታ በተደጋጋሚ ለአካባቢው አመራሮች ቢያሳውቁም
መፍትሄ ማጣታቸውን ተናግረዋል፡፡በአካባቢው አይገበሬ መሬት በብዛት ቢኖርም ባለሃብቶች አንደፈለጉ የሚያርሱበት ሁኔታ በግልጽ እታየ ነዋሪው ግን ተከልክሏል በማለት ቅሬታቸውን
ለአመራሩ አቅርበዋል፡፡
መሬት ያጡት ነዋሪዎች ለመኖር ሲሉ በኮንትሮባንድ ንግድ ተሰማርተው እንደሚገኙ የሚገልጹት ቅሬታ አቅራቢው ህብረተሰቡ ከደረሰበት እንግልትና የመልካም አስተዳደር እጦት የተነሳ
ወደ አመጽ በመሄድ  የወረዳ አመራሩን መኪና ጠብቆ በጥይት የመታበት ሁኔታ የዚሁ ማሳያ መሆኑን ገልጽው፤አሁንም መፍትሄ በአስቸኳይ የማይሰጥ ከሆነ ሁኔታው ተባብሶ ሊቀጥል ይችላል
የሚል ስጋት እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡
መሬት እያላቸው ተጨማሪ መሬት ያገኙ የወረዳ አመራሩ ሚስጥረኞች አንዳሉ ሃገሬው የሚያውቅ ሲሆን መሬት የሚሸጡ ነጋዴዎች የተፈጠሩበት አሰራር ከጊዜ ወደጊዜ መንሰራፋቱ ያሳዘናቸው
መሆኑን ተናግረው። ህጋዊ ግብር የሚከፍሉ ነዋሪዎች የሚያርሱት መሬት አጥተው በማማረር ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
በውይይቱ ለተነሱ ጥያቄዎች መልስ የሰጡት የወረዳው አስተዳዳሪ ዋናው የመልካም አስተዳደር ችግር ሆኖ ያለው መሬት  መሆኑን አምነው ችግሩን እያባባሰው ያለው አመራሩ በኪራይ
ሰብሳቢነት ዙሪያ መሰባሰቡ መሆኑን በአንክሮ ተናግረዋል፡፡ይህም ሁኔታ አይን ያፈጠጠ ህገ ወጥ አሰራሮች እየተንሰራፋበት ያለበት  መኖሩን በማመን ገልጸዋል፡፡
የወረዳው አስተዳዳሪ አክለውም በስልጣን ሽኩቻ ዙሪያ የተነሳው አስተያየትም ትክክል በመሆኑ መስተካከል እንዳለበት ተናግረዋል፡፡በአይገብሬ መሬት የተወረረውን መሬት ለመቆጣጠር
እንዳልቻሉ የተናገሩት አስተዳዳሪው በቀጣይ አጥንተን ርምጃ እንወስዳልን በማለት ዋናውን የህብረተሰቡ አንገብጋቢ የመሬት ጥያቄ ጉዳይ ወደጎን ገፋ ማድረጋቸው ህብረተሰቡን አሳዝኗል፡፡
የአካባቢው ህብረተሰብ መሰረታዊ ችግሮች ናቸው በማለት በዝርዝር ለከፍተኛ አመራሮች ቢያቀርቡም ፤በሽኩቻ ስልጣን ላይ ያሉት  በህዝብ ፊት ጥፋተኛ እንደሆኑ እየተናገሩ ምንም አይነት
እርምጃ እስካሁን አልተወሰደባቸውም፡፡ አመራሮች አሁንም ህብረተሰቡን በማንገላታት እና የራሳቸውን ጥቅም የሚገኙበትን መንገድ ይዘው በመስራት ላይ በመሆናቸው ከፍተኛ አመራሩ የመጣበት
ጉዳይ ግራ አጋብቶናል ፣ማንኛውንም ማስረጃ እንስጥ እያልን ብንጠይቅም ልመናችን ወደጎን በመተው ችግሩን ሳይፈቱ መሄዳቸው አሁንም ተጋደሉ ብሎ ለህዝቡ ፈቃድ እንደመስጠት ነው
በማለት የአካባበው ነዋሪዎች ለዘጋቢያችን ገልጸዋል፡፡             este radio

No comments: