Thursday, September 25, 2014

«ምርጫው» ምርጫ ካልሆነ መድከም ለምን አስፈለገ ? ግርማ ካሳ



የፊታችን ግንቦት 2007 ዓ.ም ምርጫ ይኖራል ተብሎ ይጠበቃል። ነገሮች ሳይበላሹና ሳይቆላለፉ ከወዲሁ እንዲታሰብበት ይችን አጭር ጽሁፍ ላቅርብ::
ምርጫ ማለት ከቀረቡ በርካታ አማራጮች መካከል አንዱን መምረጥ ማለት ነው። ሬስቶራንት ስንሄድ አስተናጋጆች ይመጣሉ። ሜኒዩ ይሰጡናል። የምግብ አይነቶች ተዘርዝረው እናነባለን።። ክትፎ፣ ጥብስ፣ ምጥን ሽሮ ..እያለ ብዙ አማራጮች ተደርድረዋል። አንዱን እንመርጣለን። ምርጫ ማለት ይሄ ነው። አማራጮች ካልቀረቡ፣ የተሰጠንን ተመገብን እንጂ መረጥን ማለት አንችልም።
በተመራጮች በኩል ሆነን ምርጫን ስንመለከት ደግሞ፣ ምርጫ ፉክክር/ዉድድር እንደ ማለት ነው። ዉድድር በሚደረግበት ጊዜ ተወዳዳሪዎቹ ተመጣጣኝ መሆን አለባቸው። የዉድድሩም የጨዋት ሕግ ሁሉም የተስማሙበትና የሚቀበሉት መሆኑ ግድ ነው። የማራቶን ሩጫ ተብሎ አንዱ በእግሩ እየሮጠ ፣ ሌላው በቢስክሌት የሚሄድ ከሆነ ፣ ይህ ዉድድር አይደለም፣ ቀልድ እንጂ። አሥራ አንድ ትጨዋሽ መሰለፍ ሲገባው አኑ ቡድን 6 ተጨዋች ብቻ ብቻ አሰልፎ የእግር ኳስ ግጥሚያ ማድረግ አይቻልም። አርባ ኪሎግራም የሚመዝን ቦክሰኛ፣ ሰማኒያ ከሚመዝን ቦክሰኛ ጋር የቦክስ ዉድድር ሲገጥም ታይቶ አይታወቅም።
ኢትዮጵያ ዉስጥ በርካታ የፖለቲካ ድርጅቶች አሉ። በምርጫ ቦርድ የተመዘገቡ ወደ ዘጠና ይደርሳሉ። ያ ችግር የለዉም። በሕዝብ ብዛት በጣም ትንሽ የሆነችዋ እስራኤል እንኳን 38 ፓርቲዎች አሏት። እንግሊዝ አገር 16 ፓርቲዎች አሉ። አሜሪካ 36 ይደርሳሉ። ነገር ግን ሶስቱንም አገሮች ካየን ዋና የሚባሉ ፓርቲዎች 2፣ 3፣ ወይንም አራት ቢሆኑ ነው።
ዋና ፓርቲዎች የሚባሉ፣ ባላቸው አደረጃጀት ጠንክረው ከሰሩና የዉድድሩ ሜዳ ነጻ ከሆነ፣ በፓርላማ መቀመጫ አግኘተው መንግስት መሆን የሚችሉ ሶስት ፓርቲዎች ብቻ ናቸው ብዬ ነው የማስበው። እነርሱም በዋናነት አንድነት ከዚያም መድረክ እና መኢአድ ናቸው።
ሰማያዊ ፓርቲ፣ ኢዴፓስ የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችላል። ኢዴፓ ካለፈው የ2002 ምርጫ በኋላ ድራሹ ጠፍቷል። አቶ ሙሼ ሰሙ በተለያዩ ጊዜ ኢዴፓን ወክለው በተሳተፉበት ዉይይቶች ምክንያት ፣ እንዲሁም አቶ ልደቱ አያሌው ለአዲስ አድማስና ለአዉራምባ ታይምስ አንድ ወቅት ቀርበው አስተያየት በሰጡበት ጊዜ ፣ ስለኤደፓ ከሰማነው ዉጭ ፣ ምንም አይነት እንቅስቃሴ ሲደረግ የሰማንበት ሁኔት የለም። ይህም በራሱ የድርጅቱን መክሰም የሚያመላክት ነው። እንደዉም ለበርካታ አመታት ድርጅቱን ሲመሩ የነበሩት አቶ ሙሼ ሰሙም ፣ በፍቃዳቸው ኢዴፓን እንደለቀቁም አንብበናል።
ሰማያዊ ፓርቲ ጥሩና አስደሳች ጅማሬ ነበረው። ከአንድ አመት በፊት በጠራው ሰላማዊ ሰልፍ በአንድ ቀን ብቻ ወደ ሰባ ሺህ የሚሆን ሕዝብ ለመሰብሰብ ችሎ ነበር። በዉጭ አገር እንደ ዶር አለማየሁ ገብረማርያም፣ በአገር ዉስጥ ደግሞ እንደ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ያሉ ምሁራንን ድጋፍ እስከማግኘት የደረሰ ድርጅት ነው። በአለም አቀፍ ማህበረሰቡም ዘንድ በአጭር ጊዜ ዉስጥ ስሙ ሊገን ከመቻሉ የተነሳ በዉጭ ዲፕሎማቶች ተጋብዘው የድርጅቱ ሊቀመንበር ንግግር ያደረጉበት ሁኔታ ተፈጥሮም ነበር። ሰማያዊ በርግጥ ትልቅ ፖቴንሻል የነበረው ድርጅት ነበር።
ነገር ግን በአንድ አመት ጊዜ ዉስጥ በሊቀመንበሩ ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት በርካታ ስህተቶችና የአመራር ድክመት፣ የድርጅቱ ተቀባይነት ወደ ታች በጣም አሽቆልቁሏል። ሰባ ሺህ ሕዝብ ያስወጣ ድርጅት፣ ከጥቂት ወራት በፊት በአዲስ አበባ ባደረገው ሰልፍ ሶስት መቶ ሰው ብቻ ነበር የወጣለት። ( በወቅቱ መድረክ ከሃያ ሺህ አንድነት ደግሞ ከመቶ ሺህ በላይ ሕዝብ በጠሯቸው ሰልፎ ተገኝተዉላቸው ነበር)
ይሄ ብቻ አይደለም፣ ሰማያዊ ከአዲስ አበባ ዉጭ ይሄ ነው የሚባል ድርጅታዊ መዋቅር የለዉም። በአርባ ምንጭ እና በድረደዋ አንዳንድ ስራዎች ተሰርተዋል። ከዚህ ዉጭ ብዙ ገፍቶ መሄድ አልቻለም። በድርጅቱ ዉስጥም በሊቀመንበሩ አመራር ዙሪያ በርካታ ልዩነቶች እየታዩ ነው። በድርጅቱ ዉስጥ ትልቅ አለመስማማት አለ። እንደዉም ብዙዎች የሰማያዊ ፓርቲን ጥለው ሌሎች ድርጅቶችን (በዋናነት አንድነትን) ሊቀላቀሉ ይችላሉ የሚል ወሬም አለ። ስለዚህ ሰማያዊ ምናልባት ያሉትን ችግሮች አስተካክሎ፣ አዲስ አመራር አፍልቆ ፣ ብስለት በተሞለ መልኩ የፖለቲክ ስራዉን በቶሎ ካልጀመረ በቀር የትም ይደርሳል ብዬ አላስብም። (ያው በፌስ ቡክ ከመለቅለቅ ዉጭ) ባለኝ ግምት ሰማያዊ አሁን ባለበት ሁኔታ፣ ልወዳደር ቢል ሊያሰልፍ የሚልችለው ከ547 የፓርላማ ወንበሮች ፣ ከ50 ተወዳዳሪዎች የሚበልጥ አይሆኑም።
የአንድነት ፓርቲ እና መኢአድ (እንደ ትብብር ያሉ ሌሎች ድርጅቶችን በማቀፍ) ለምሳሌ በደቡብ ፣ በአዲስ አበባ፣ በአማራው ክልል ባሉ ሁሉም ወረዳዎች ( 284 ) ፣ በኦሮሚያ ባሉ ስድሳ በመቶ የሚሆኑ ወረዳዎች (110) ፣ በትግራይ ክልል አምሳ በመቶ በሚሆኑ ወረዳዎች ( 19) እንዲሁም በሌሎች ክልል ባሉ የተወሰኑ ወረዳዎች፣ በአጠቃላይ ከ450 ወረዳዎች በላይ ተወዳዳሪዎችን የማሰለፍ አቅም አላቸው። መድረክ በአዲስ አበባ፣ ኦሮሚያና በትግራይ ባሉ ወረዳዎች በሙሉ፣ በደቡብ ግማሹን በአጠቃላይ ወደ 300 ወረዳዎች ተወዳዳሪዎች ማሰለፍ የሚችል ይመስለኛል።
ለዚህም ነው፣ የዉድድሩ ሜዳ ፍትሃዊና ነጻ ከሆነ፣ አንድነት/መኢአድ፣ መድረክ በመጪው የ2007 ጠንካራ ተወዳዳሪ ሆነው ሊቀርቡ የሚችሉበት ሁኔታ በጣም ሰፊ ሊሆን ይችላል የምለው። የፊታችንም ምርጫ፣ በርግጥ ለአገር የሚጠቅም፣ ሕዝቡ ፍላጎቱን በሚገባ የሚያንጸባርቅበት፣ ታላቅና ታሪካዊ ምርጫ የሚሆንበት ሁኔታ ይፈጠር ነበር።
ነገር ግን ሕወሃት/ኢሕአዴግ ከወዲሁ ምርጫዉን፣ ዋጋ ቢስ እያደረገው ነው። ችግሮቻችን በምርጫው፣ በሰላም ፈተን፣ እንደ አገር ተያይዘን ወደፊት የምንሄድበትን መልካም አጋጣሚ እያጨለመብን ነው። ጠንካራ ተወዳዳሪ መሆን የሚችሉ ድርጅቶች ላይ ከፍተኛ ወከባ እየተፈጠረ ነው። የአመራር አባላቶቻቸው ወደ ወህኒ ተወስደዋል። ጋዜጦቻቸው እንዲዘጉ ተደርጓል። ጠዋትና ማታ በኢቲቪ በባለስልጣናቱ ማስፈራሪያ ይደርስባቸዋል። ሊዋሃዱ፣ የበለጠ አብረው ሊሰሩ ሲሞክሩ፣ ምርጫ ቦርድን በመጠቀም የዉህደት እንቅስቃሴያቸውን ያስቆማል። ሰላማዊ ሰልፎችን ፣ ሕዝባዊ ሰብሰባዎች ለማድረግ ሲሞክሩ፣ ፍቃድ ይከለክላል፣ ፍቃድ ተሰጥቶም ቅስቀሳ ሲደረግ ቀስቅቃሾቹን ያስራል። በዚህ ሁኔታ የሚደረግ ምርጫ ምርጫ አይደለም።
ሕወሃት/ኢሕአዴግ በአስቸኳይ ምርጫዉ ዴሞክራሲያዊ፣ ፍትሐዊና ነጻ እንዲሆን ለማድረግ በተግባር ቁርጠኝነቱን ሊያሳይ ይገባል። የታሰሩ ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮች ፣ የፖለቲክ መሪዎች በሙሉ መፈታት አለባቸው። ግንቦት ሰባት፣ ኦነግ ተብለው ነው የተከሰሱት። ሰሞኑን በስፋት በአንዳንድ ሜዲያዎች እንደሚዘገበውም ኦነግም ሆነ ግንቦት ሰባት ከኤርትራ ጋር ሆነው እናደርገዋለን የሚሉት ሽምቅ ዉጊያ እንደሌለ ነው የተረዳነው። ኦነግም ሆነ ግንቦት ሰባት ምንም አይነት አደጋ ሊፈጥሩ እንደማይችሉ፣ ከአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ዉጭ የታሰሩ እስረኞችም ምንም አይነት ግንኙነት ከነዚህ ድርጅቶች ጋር እንደሌላቸው ያውቃሉ።
ይልቅስ አገርን ትልቅ አደጋ ላይ የሚጥለው፣ ሕወሃት/ኢሕአዴግ እራሱ እየወሰደ ያለው አፋኝ ተግባራቶቹ ናቸው። እንደ ዘጠና ሰባት ወይንም እንደ 2002፣ እነርሱ በብስኪሌት እየሄዱ ሌላው በእግሩ እየሮጠ የሚደረግ ዉድድር አሸንፈው፣ ተመረጥን ብለው፣ በኃይል ለመግዛት ያሰቡና እየዶለቱ ያለ ይመስላል። ቆም ብለው እንደገና እንዲያስቡ እመክራቸዋለሁ። በዉስጣቸው ያሉ ከጫካ ፖለቲካ ነጻ ያልወጡ አክራሪዎች ገደል ይዘው እንዳይከቷቸው መጠንቀቅ አለባቸው። ለነርሱም ለአገርም የሚያዋጣው፣ መጪው ምርጫ ሰላማዊ፣ ፍትሃዊ፣ ዴሞክራሲያዊና በሁሉም ወገኖች ተቀባይነት ያለው ምርጫ እንዲሆን ማድረጉ ብቻ ነው።
ከአንድነት/መኢአድ፣ መድረክ ከመሳሰሉት ጋር በቁም ነገር ቁጭ ብሎ መነጋገር ያስፈልጋል። እነ ሃብታሙ አያሌው፣ አብርሃ ደስታ፣ የሽዋስ አሰፋ፣ ዳንኤል ሺበሺ፣ አንዱዋለም አራጌ፣ ናትናኤል መኮንን፣ በቀለ ገርባ ..ያሉ የፖለቲካ መሪዎች፣ እንደ እስክንደር ነጋ፣ ርዮት አለሙ፣ ዉብሸት ታዬ፣ ዞን ዘጠኞች …ያሉ ጋዜጠኖችን እና ብሎገሮችን የግድ መፈታት አለባቸው። የነዚህ ወገኖቻችን መታሰር የአገር ደህንነትን የሚከላከል ሳይሆን የአገር ደህንነትን አደጋ ላይ የሚጠል ነውና ። እንደ ፍኖት ነጻነት፣ ፍትህ የመሳሰሉ ጋዜጦች እንዲታተሙ መፈቀድ አለበት።
ኳሷ በሕወሃት/ኢሕአዴግ ሜዳ ላይ ነው ያለችው ። ጊዜው በጣም ተለዉጧል። ነገሮች በጣም ተወጥረዋል። ባለስልጣናቱ ሃብታሞችና የሥርዓቱ ተጠቃሚዎች በስፋት የሚኖሩባት ምስራቅ አዲስ አበባ እየኖሩ፣ በሕዝቡ ልብ ዉስጥ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያመረቀዘ ያለዉን ቁስል ላያስተዉሉ ይችላሉ። ምናልባትም ከታች ያሉት ካድሬዎቻቸው መስማት የሚፈልጉትን ብቻ ስለሚነግሯቸው ፣ «ባለንበት ገፍተን እንቀጥል ። ሁሉ አማን ነው» በማለት በሩን ሊቀረቅሩት ይችላሉ። ነገር ግን ደግሜ እላለሁ ቢያስቡበት ይሻላል።
አገር ቤት ላሉ ተቃዋሚዎች ደግሞ የሚከተለዉን መልእክት አስተላልፋለሁ፡
የምርጫ ፓርቲ ናችሁ። ነገር ግን በባዶ እግራችሁ ብስክሌት ከያዘ ጋር እንወዳደራለን ብሎ መነሳት፣ ራሳችሁን ከማስገመት በተጨማሪም ለገዢው ፓርቲ የፖለቲካ ፍጆታ መጠቀሚያ ብቻ ነው የምትሆኑት። ምርጫ የምትሳተፉ ከሆነ፣ የምርጫ ዘመቻ ማድረግ አለባችሁ። ምርጫው ሰባት ወራት ነው የቀሩት። በሚቀጥለው አንድ ወራት ዉስጥ አገዛዙ ነገሮችን ካላስተካከለ ፣ በምርጫ መወዳደራችሁ ፋይዳ አይኖረውም። እንዴት ብላችሁስ ነው የምርጫ ዘምቻ የምታደርጉት ? መልእክቶቻችሁን እንዴት ነው ለሕዝብ የምታቀርቡት ? ከሕዝብ ጋር በነጻነት ካልተገናኛችሁ፣ ጋዜጣ ካላተማችሁ ፣ ሽብርተኞች እየተባላችሁ ከታሰራችሁ እንዴት ምርጫ ልትሳተፉ ትችላለችሁ ? ምርጫው በአንጻራዊነት ሰላማዊና ተቀባይነት ያለው እንዲሆን ፣ በጋራ፣ ባሉ መስመሮች ሁሉ አገዛዙ ላይ ጫና ማድረግ መጀመር አለባችሁ። ሕወሃት/ኢሕአዴግ ዉስጥ ያሉ ሞደሬቶችን በማሳመን እና በማግባባት፣ ሊፈጠር የሚችለውን አደጋ በማሳየት፣እነርሱ በፊናቸው በፓርቲያቸው ዉስጥ ለዉጥ እንዲመጣ ግፊት እንዲያደርጉ ማበረታታቱ አስፈላጊ ነው። በአንድ ወር ጊዜ ዉስጥ ነገሮች ካልተስተካከሉ፣ የጠራ የአቋም በጋራ በመዉሰድ፣ በምርጫው እንደማትሳተፉም መግለጽ ይኖርባችሁል። ዋጋ ለሌለው ነገር ፣ ምርጫ ፣ ምርጫ እየተባለ ጉልበት፣ ጊዜና ገንዘብ ማጥፋት አያስፈልግም። ሕዝቡ አማራጮች ነጻ በሆነ መንገድ እንዲቀርቡለት ካልተደረገ ፣ ነጻነቱን እና መብቱን የሚያረጋግጥበት የራሱ የሆኑ ሌሎች መንገዶችን ይፈለጋል።                           sourse abugda

No comments: