Wednesday, April 30, 2014

UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ) በሰፊው የኦሮሞ ህዝብ እና ልጆች ላይ እየተፈፀመ ያለውን ግፍ በአጽንኦት እናወግዛለን!!!

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)

wellega
ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ በኢትዮጵያ የመሬት ስሪት ላይ ግልፅ አቋም እና ፖሊሲ ያለው ፓርቲ መሆኑ ከማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ በዚህም መሰረት መሬት በሦስት መሰረታዊ አውድ ላይ እንዲመሰረት ይህም ማለት በወል፣ በመንግስትና በግል ይዞታነት እንዲከበር አቋም ይዞ ይታገላል፡፡ ነገር ግን ከወልና ከመንግስት ውክልና ውጪ ያሉት ይዞታዎች በግል ይዞታነት እንዲከበሩ አቋም ይዞ ይታገላል፡፡ ኢህአዴግ የገጠሩ መሬት የግል ከሆነ አርሶ አደሩ መሬቱን እየሸጠ ወደ ከተማ ይፈልሳል ብሎ ያምናል፡፡ ከምንም የተነሳ ስጋት ነው ባይባልም አንኳ ኢትዮጵያውያን ከመሬት ጋር ያለንን ስነልቡናዊ፣ ማህበራዊና ሁለንተናዊ መስተጋብርን ያላገናዘበና የተጋነነ ስጋት ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን ከመሬት ጋር የተለየ ቁርኚት እንዳላቸሰው ለማወቅ ሞታቸውን ሲያስቡ እንኳ “የሀገሬ አፈር ይብላኝ” ሲሉ መመኘታቸው በቂ ማስረጃ ነው፡፡ ኢህአዴጎቹም በቀድሞ ስርዓት ሲተገበር የታገሉትን የመጨቆኛ መሳሪያ ለራሳቸው ሲሆን ተጠቀሙበት፡፡ የሆኖ ሆኖ ይህ የኢህአዴግ ስጋት እውነት ነው እንኳ ቢባል ኢህአዴግ የከተማውን መሬትስ የግል ይዞታ ያላረገው ከተሜው ወዴት እንዳይሰደድ ነው?
ዋናው የገዥው ፓርቲ ፍላጎት መሬትን በጁ በማድረግ የዜጎችን ነፃነት በዚያኑ ያክል ለመሸበብ ነው፡፡ አርሶ አደሩም ሆነ የከተማው ህዝብ መሬት የኔ ነው ብሎ ካመነ ለኢህአዴግ ጫና ስለማያጎበድድ መያዣ ለማድረግ ነው፡፡ የህዝቡ የመሬት ባለቤትነት ቢረጋገጥ በመንግስትና ለኢንቨስትመንት በሚፈለጉ መሬቶች ላይ የመደራደር አቅሙ እጅግ ከፍ ይላል፡፡ መሬቱን በመልቀቁ በሚሰጠው ካሳ (ዋጋም) በቂ የኑሮ ዘዬ ሽግግር የሚያገርግበት አጋጣሚ ይፈጥራል፡፡ ይህ ሊሆን አልቻለም፡፡ በ02/ 08/ 06 ዓ.ም ቡራዩ አካባቢ በተደረገ የመሬት የሊዝ ጨረታ ለተነሺው አርሶ አደር በካሬ 10 ብር የታሰበለት መሬት በጨረታ በካሬ 17 ሺህ ብር መሸጡን ፓርቲያችን ያሰባሰበው ማስረጃ ያሳያል፡፡ በ10 ብር የታሰበለት አርሶ አደር የሚሰደደው በዚህ መልኩ መንግስት ሲቀማው እንጂ የመሬቱ ባለቤት ሆኖና ተደራድሮ በሚሸጥበት ወቅት አልነበረም፡፡
መሬት የምርጫ ድምፅ መያዣ፣ ለኢህአዴግ ገንዘብ ማሰባሰቢያ እና የድጋፍ ምንጭ ሆኗል፡፡ በቅርቡ በጉጂ ዞን ኦዶ ጉዶ አካባቢ ለ2007 ዓ.ም ምርጫ ሞዴል የተባሉ አርሶ አደሮች በቁጥር ከፍ እንዲሉ እንደሹመት ተሰጥቷቸው ሲያበቃ 500 ብር እንዲያዋጡ የመሬት ይዞታቸው ለማስፈራሪያነት መዋሉ እንደማሳያ ሊወሰድ ይችላል፡፡
በሌላ በኩል ምንም አይነት ህዝባዊ ውይይት ሳይደረግበት ከሰማይ ዱብ ያለው የአዲስ አበባ እና ኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ የልማት መሪ ፕላን ያስቆጣቸው የኦሮሞ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ሰልፍ በማድረጋቸው የደረሰባቸውን ህገ ወጥ ድብደባና እስራት አንድነት በእጅጉ ይቃወማል፡፡ ለእውነተኛ ልማት ነው እንኳ ተብሎ ቢታሰብ ኢህአዴግ ካለበት የተአማኒነት ችግር የተነሳ ተማሪዎቹ ለተቃውሞ አደባባይ ቢወጡ ተፈጥሯዊ እና ህገ መንግስታዊ መብታቸው ሊከበር በተገባ ነበር፡፡ ነገር ግን ሁሉን ነገር ካልጋትኳችሁ የሚለውና ለዴሞክራሲያዊ ሽንፈት የማይገዛው ኢህአዴግ በተማሪዎቹ ላይ ያደረሰውን እንቃወማለን፡፡ የታሰሩ ተማሪዎችም በአስቸኳይ እንዲፈቱም እንጠይቃለን፡፡ የኦሮሞ ተማሪዎችን በገፍ ከዩኒቨርሲቲ የትምህር ገበታቸው በማባረር የሚታወቀው የኢህአዴግ መንግስት ከዚህ ተደጋጋሚ ተግባሩ ታቅቦ ልጆቹን በአስቸኳይ ወደ ትምህርት ገበታቸው እንዲመልስ እንጠይቃለን፡፡
በአጠቃላይ መሬት የዜጎች መያዣ መሆኑ እንዲቀር እንታገላለን፡፡ ዜጎች በመሬታቸው የመደራደር እውነተኛ መብት ሊኖራቸው ይገባል፡፡
ተቃውሞ የሚያነሱ ዜጎችም ድምፅ እንዲሰማ እናሳስባለን፡፡

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ
ሚያዚያ 22 ቀን 2006 ዓ.ም
አዲስ አበባ

No comments: